Thursday, November 5, 2015

የኢ.ፌ.ድ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር በሁለተኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ዙሪያና የ2008 ዓ.ም የመጀመሪያው ሩብ አመት አፈጻፀምን አስመልክቶ በዘርፉ ከተሰማሩ ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አደረገ፡፡



 በዕለቱም በርካታ በዘርፉ የተሰማሩ ባለድርሻ አካላት የተገኙ ሲሆን አዲስ ከተሾሙት የኢ.ፌ.ድ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሀመድና የባህል ዘርፍ ሚኒስቴር ዴኤታ ከሆኑት ወ/ሮ መአዛ ገብረመድህን ጋር ትውውቅ አድርገዋል፡፡
 በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የፖሊሲ እቅድ ዝግጅት ባለሞያ የሆኑት አቶ ባህረዲን መንሱር ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የመጀመሪያው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ግቦች፣ የዕትዕ አፈፃፀም በጥቅል ከባህል ልማት፣ ከቱሪዝም ገበያና ልማት አንፃር እና ሌሎች አበይት ተግባራት ፣ ያጋጠሙ ችግሮችና የተወሰዱ መፍትሄዎች የነበሩ ድክመቶችና ጠንካራ አፈፃፀሞች ላይ እንዲሁም የ2ኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን ምን ምን ዕቅዶች አካቷል የሚለውንና የ2008 በጀት ዓመት ዕቅድ የተቀመጡ የትኩረት አቅጣጫዎችን ለባለድርሻ አካላት አቅርበዋል፡፡ በመጀመሪያው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዙሪያ በአጠቃላይ የተከናወኑት ተግባራት ሲፈተሸ እና ሲገመገም የተሰራው ስራ የመጀመሪያው ምዕራፍ በስኬት መጠናቀቁን እንደሚያሳይ ገልፀዋል፡፡

በቀረቡት አሳቦች ላይ በዘርፉ ከተሰማሩ ባለድርሻ አካላት በርካታ አስተያየቶችና ጥያቄዎች ተነስተው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡
የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሀመድ ለሀገር ተጨባጭ የሆነ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ፋይዳ ያላቸው ተግባራት ከሚከናወኑበት ሴክተር በመቀላቀላቸው ደስታቸው ከፍ ያለ መሆኑንና በመንግስት ወገን የሚደረግ የተናጠል ሩጫ ብቻውን ለውጤት የሚያበቃ ስለማይሆን የዘርፉ ባለድርሻ አካላት ሁለንተናዊ ተሳትፎና በቁርጠኛ አገራዊ ስሜት የታጀበ ድጋፍ ሊጠናከር እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ አክለውም በዕቅዱ ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ የተደረገው ውይይት በቀጣይ በየዘርፉ እንደሚቀጥልና የተነሱ አሳቦችና አስተያየቶች ላይ በጋራ በመስራት ሊሻሻሉ የሚገባቸው ነገሮች ላይ በማተኮርና ውጤት የታየባቸውን ስራዎች አጠናክሮ በመቀጠል በሲስተም መመራት የሚችል ዘርፍ እንዲኖር ጥረት እናደርጋለን በማለት ሲገልፁ፡፡ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ዴኤታ ወ/ሮ ታደለች ዳለቾ በበኩላቸው ባቀድንበት ደረጃ በነበረው አቅም በጋራ በሰራንባቸው ጉዳዮች ላይ በአፈፃፀማችን 90% ፈፅመናል ካቀድነው አንፃር ጥሩ ቦታ ደርሰናል የሚቀሩን ነገሮች ቢኖሩም ከባለድርሻ አካላት ግብዓቶች አሰባስበን በቀጣይ ውይይት በማድረግና በለየናቸው የትኩረት መስኮች ላይ የተለያዩ ተግባራትን እናከናውናለን ብለዋል፡፡ የባህል ዘርፍ ሚኒስቴር ዴኤታ ወ/ሮ መአዛ ገብረመድህን አብዛኞቹ የተነሱት አሳቦች ለዕቅዱ ግንባታ የሚሆኑ ነገሮች ናቸው በየዘርፉ በምናካሄድባቸው ውይይት አብረን ዳር የምናደርስበት ባህልና ቱሪዝምን ወደተሻለ እድገት የምናራምድበት ይሆናል ብለዋል፡፡
ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በቀጣይ በስራ ሂደት ለሚገጥሙ ተግዳሮቶች በመመካከር ችግሮችን ለመፍታት እንደሚንቀሳቀስና በሁለተኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን በጋራ በመስራት የባህልና ቱሪዝም ዘርፉን ወደላቀ ደረጃ እንደሚያደርስ ተገልፃል፡፡

No comments:

Post a Comment