Wednesday, August 19, 2015

ኢትዮጵያ ሁለተኛውን የእድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ስትጨርስ፤
ዓመታዊ የጎብኚዎቿን ቁጥር 2.16 ሚሊዮን ለማድረስ አቅዳለች፡፡
በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ የመጣው የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ከፍተኛ ገቢ እያስገኘ መጥቷል፡፡ የፈረንጆቹ 2012 ዓመት 1 ቢሊዮን ያክል ጎብኚ የቱሪስት ፍሰት ተመዝግቦ 1.03 ትሪሊየን ዶላር ገቢ ተገኝቷል፡፡ ከዚህ ውስጥ በዚሁ ዓመት አፍሪካ ድርሻ 34 ቢሊዮን ዶላር ነበር፡፡ ሀገራችን የመጀመሪያውን የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ስታጠናቅቅ በ750 ሺ የውጪ ጎብኚዎች ተጎብኝታ ያገኘችው ገቢ 2 ቢሊየን ብር ደርሶ ነበር፡፡


ባሳለፍንው ሳምንት የኦሮሞ ብሔረሰብ ዞን መዲና ከሚሴ የሀገራችንን የቀጣዩ አምስት ዓመታት የቱሪዝም ልማት እቅዶች ላይ የሚመክር ጉባኤ አስተናግዳ ነበር፡፡ በዓለም የቱሪዝም ተወዳዳሪነት 120ኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው ሀገራችን ከአፍሪካ 17ኛውን ደረጃ ይዛለች፡፡ የቀጣዮቹ አምስት ዓመታት እቅድ ይህንን ወደ ተሻለ ደረጃ ሊያሻግሩ እንደሚችሉ የብዙዎች እምነት ነው፡፡ አሁን ከሃያ ሺ የማይበልጡ የመኝታ ክፍሎችና 25 ሺ ገደማ አልጋዎችን ይዛ ጎብኚዎችን የምታስተናግደውን ሀገር በአምስት አመቱ መጨረሻ የ58 ሺ የመኝታ ክፍሎች ባለቤትና 104 ሺ ገደማ አልጋዎች የሚገኙባት ሀገር ለማድረግ ታቅዷል፡፡ ከዚህ ውስጥ ደረጃ ያላቸው ሆቴሎችን ቁጥር በእቅዱ ዓመት መጨረሻ ወደ 800 የማድረስ ሶስት ብቻ የሆኑትን ዓለም አቀፍ ብራንድ ባለቤት ሆቴሎች ወደ 12 ከፍ ለማድረግ የታሰበ ነው፡፡
ጉባኤው በእቅዶቹ ላይ በስፋት መክሯል፡፡ ከአምስት ዓመታት በኋላ ሀገሪቱ ከቱሪዝም የምታገኘውን ገቢ 6 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ የጋራ መግባባት የተያዘበት ጉባኤ ነበር፡፡

No comments:

Post a Comment