Wednesday, April 1, 2015



2ኛው የግዕዝ ጉባኤ በባህር ዳር ተካሄደ፡፡

በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የቋንቋና ባህል እሴቶች ልማት ዳይሮክተሬት የተዘጋጀውና ከመጋቢት 22 ቀን እስከ መጋቢት 22 ቀን 2007 ዓ.ም ሁለት ቀናት የቆየው 2ኛው ሀገር አቀፍ የግእዝ ጉባኤ በስኬት ተጠናቀቀ፡፡ በባህር ዳር ከተማ የተካሄደው ይህ ጉባኤ በርካታ ምሁራን፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመራማሪዎች፣ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት፣ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎችን ጨምሮ ጉዳዮ የሚመለከታቸው አካላት ታድመውበታል፡፡
ጉባኤው በሁለት ቀናት ቆይታው ስምንት የሚደርሱ የውይይት መነሻ የጥናት ጽሑፎች ቀርበውታል፡፡ እነዚህም በቅድመ ክርስትና ተቀርጸው የተገኙ የድንጋይ ላይ ጽሑፎች ለኢትዮጵያና ለአካባቢው ያላቸው ታሪካዊ ፋይዳ፣ ጥንታዊ የብራና ጽሑፎች እንደ ሰነዶች ምዝገባና ማረጋገጫ ጽ/ቤት፣ የግዕዝ ሥነ-ጽሑፍ ጥቅም ለመካከለኛው ኢትዮጵያ ጥናት፣ ባህረ ሀሳብና ግዕዝ፣ የግዕዝ ቅኔና ፍልስፍናው፣ የግዕዝ ቋንቋ ትምህርት በአራቱ አድባራት ወ ገዳማት፣ ግዕዝና ሥነ-ጽሑፍ የሚሉ ርዕሶች ላይ ያተኮሩ የጥናት ጽሑፎች ናቸው፡፡
ዝግጅቱ ታሪካዊ የሆኑትንና በቅኔና አብነት ትምህርት ተቋምነታቸው የሚታወቁትን የምስራቅ ጎጃም ጥንታዊ አድባራትን የመጎብኘት መርሀ ግብርን አካቷል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ የባህል ማእከልና ሌሎች አካላት የዝግጅቱ አጋሮች በመሆን ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል፡፡ አንደኛው የግዕዝ ጉባኤ አምና በተመሳሳይ ወቅት በአክሱም ከተማ መካሄዱ ይታወሳል፡፡

No comments:

Post a Comment