Tuesday, June 5, 2012

                 አንድ ሺሕ አምስት መቶ ዓመት ያስቆጠረው የአቡነ ገሪማ ገዳም
                                              ሙዚየም ተመረቀ
አንድ ሺሕ አምስት መቶ ዓመታት ባስቆጠረው የአቡነ ገሪማ ገዳም የተሠራው አዲስ ሙዚየም ግንቦት 18 ቀን 2004 ዓ.ም. ተመረቀ፡፡
በትግራይ ክልል በዓድዋ ወረዳ የሚገኘውና ከገዳሙ እኩል ዕድሜ 1500 ዓመታትን ያስቆጠረ የወንጌል መጻሕፍትና ጥንታውያን ቅርሶች ላሉበት ገዳም ዘመናዊ ሙዚየሙ የተገነባለት ከ400 ሺሕ ብር በላይ ወጪ ነው፡፡

መምህር ዳንኤል ሰይፈ ሚካኤል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቱያን የቅርስ ጥበቃና ምዝገባ የቤተ መጻሕፍት ወመዘክር መምርያ ኃላፊ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የፈረንሣይ መንግሥት በሰጠው ከ400 ሺሕ ብር በላይ ዕርዳታ መሠረት ጥንታዊው ሕንፃ ታድሶና ተዘጋጅቶ ለቤተ መዘክር አገልግሎት እንዲውል ተደርጓል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ በምረቃው ላይ ባደረጉት ንግግር፣ ከጥንት ጀምሮ እጅግ ሰፊና ተነግሮ የማያልቅ ታሪክ ያላት፣ በቅዱሳት መጻሕፍት በተደጋጋሚ ስሟ የተጠራ፣ በብሉይ ኪዳን የታቦተ ጽዮን መገኛ፣ በሐዲስ ኪዳንም ክርስትናን ከሁሉም ቀድማ በመቀበል የዓለም ትላልቅ ሥልጣኔዎች መሪ እንደነበረች አስታውሰው፣ የእነዚህ ጥንታውያን ታሪኮችና ገድሎች ምስክር የሚገኝባቸው ገዳማትና አድባራት በተራራና በሐይቆች በዱርና በሸለቆዎች ውስጥ ቢገኙም፣ አሁንም ጥንታዊ ይዞታቸውን እንደጠበቁ የሚገኙ ስለሆነ፣ ለከፍተኛ ምርምርና የቱሪዝም መስሕብነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ስላላቸው ወደ እነዚህ ቦታዎች ለመድረስ መንገድና የመሠረተ ልማት አውታሮችን ለማሟላት የሚመለከታቸው አካላት ሊያስቡበት ይገባል በማለት ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡

አባ ገሪማ ገዳም ለገዳሙ መነኰሳትና ለኢትዮጵያ ክርስቲያኖችና ለኢትዮጵያውን ሁሉ ብቻ ሳይሆን ለመላው ዓለም የሰው ልጅ ታሪክ እጅግ ጠቃሚና አስፈላጊ ቅርሶችን ጠብቆ የቆየ ገዳም በመሆኑ ሙዚየሙ መሠራቱን ያወደሱት በኢትዮጵያ የፈረንሣይ መንግሥት አምባሳደር ሚስተር ጃን ክሪስቶፍ ቢልያር፣ የገዳሙን ብርቅዬ ቅርሶችን በመላው ዓለም ለማስተዋወቅ ሙዚየሙ ዓይነተኛ መሣርያ መሆኑን አመልክተዋል፡፡

መምህር ዳንኤል ለሪፖርተር እንዳብራሩት፣ በአምስተኛው ክፍለ ዘመን ከዘጠኙ ቅዱሳን አንዱ በሆኑት በጻድቁ አቡነ ገሪማ የተመሠረተው የአቡነ ገሪማ ገዳም፣ በዓለም እጅግ ጥንታውያን የሚባሉና የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሆኑት የወንጌል መጻሕፍትን ጠብቆ ያቆየ ገዳም ነው፡፡ ገዳሙ ካሉት ቅርሶች መካከል አቡነ ገሪማ እንደጻፏቸው (እንደገለበጧቸው) በሚታመኑት ወንጌሎች ውስጥ ያሉት ሥዕሎችም ረቂቅ የሥነ ሕንጻ ሥነ ጥበብን፣ በአውሳብዮስ የተዘጋጀውን የሥርዓተ ቀኖና ዘቅዱሳት መጻሕፍት ከኑባሬ ሥርዓቱ ጋር፣ እንዲሁም የወንጌላውያኑን ምስል ከምሳሌዎቻቸው ጋር ያሳያሉ፡፡ እነዚህ ሁለት መጻሕፍት በትውፊቱ መሠረት አቡነ ገሪማ እንደጻፉአቸው ቢታወቅም፣ በሳይንሳዊ መንገድ ለማረጋገጥ በካርበን ዴት አማካይነት ዕድሜን ለማወቅ በሚያስችል የጥናት መሣሪያ ታይቶ በትክክልም የአምስተኛውና የስድስተኛው ክፍለ ዘመን መጻሕፍት እንደሆኑ መረጋገጣቸውን መምህር ዳንኤል ገልጸዋል፡፡

ሙዚየሙ ካቀፋቸው ጥንታውያን ቅርሶች መካከልም በኢትዮጵያ ውስጥ እጅግ አስገራሚ የሆነው በዙርያው በአስደናቂ ሁኔታ የተሣሉ ቅዱሳት ሥዕሎችን የያዘ ጽዋ፣ በአሠራሩና በውበቱ ልዩ የሆነ እርፈ መስቀልና በማምሉክ ሡልጣኖች ዘመን (1338 ዓ.ም.) እንደተሠራ የሚታመን ልዩ ዐውድ ይገኙበታል፡፡

የሙዚየሙ የ20ኛው ክፍለ ዘመን ክፍልም የንግሥተ ነገሥታት ዘውዲቱንና የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ልዩ ልዩ ሥጦታዎችና ቅርሶች ከቀደምት አባቶች ፎቶ ግራፎችና ታሪኮች ጋር አብረው እንደሚታዩ ኃላፊው ገልጸዋል፡፡

ሙዚየሙን መርቀው የከፈቱትም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያና በኢትዮጵያ የፈረንሣይ አምባሳደር ሚስተር ጃን ክሪስቶፍ ቢልያር ናቸው፡፡ በሥነ ሥርዓቱ ላይ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የባህልና የትምህርት አማካሪ ሚኒስትር ፕሮፌሰር አንድርያስ እሸቴ ተገኝተዋል፡፡

No comments:

Post a Comment